Tuesday, April 16, 2013

ሰላም ላንተ


ሰላም ላንተ ይሁን ከእናትህ ጉያ ወጥተህ እዳሪ መሬቷን ሳታርስላት ፣ አባትህ አቅሙ በደከመ ጊዜ ሳታግዘው ለተለየሃቸው፣ ምሽትህ ምሰሶዋ ሆነህ ሳትጠግብህ በስስት ለራቅካት ልጆችህ ቤት ሲገቡ ሞገሳቸውን አንተን ላጡ ላንተ ሰላም ላንተ ለወታደር ፤ ወጥቶአደር ሁሌም ድንበር ሉዐላዊነታችንን የምትጠብቅ የያዝነውን የማታስነጥቅ ከጥንት እስካን በተወራረሰ የደም እና የወኔ ውርስ የታተምክና የተሰራህ ለእኛ ሰላምና ለበላዮችህ ሰላምታ ስትሰጥ ስትደክም ለምትኖር ላንተ፤
ሰላም ላንተ ጦርነት ካልመጣና የሹመኞችህ ወንበር ካተነቀነቀ በቀር ትውስታ ውስጥ ለማትገባው፣ በየጊዜው በግምገማ ግራ ለምትጋባው፣ እኛ ለመኖር ስንታትር አንተ ለመሞት የቆረጥከው ላንተ፤
ለሹመኞቹ ሰላምታችን ሁሉ ባንተ ተጠቃሎ ስለሚደርስልን መጥቀስ አያስፈልገንም ነገር ግን ከልብ የመነጨ ኩራታችንን እሳቱ ላይ ለምትጣደው የአዳምና የሔዋን ዘር እናቀርባለን፡፡
በዚህ ሰሞን የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. መከላከያ ሠራዊት ቀን ወይንም ሳምንት እየተከበረ ነው እናም ግራ የሚያጋባ ስሜት ተሰማኝ ምክንያቱም ኢትዮጵያ እስካሁን የቆየችው ከላይ የተጠቀሰውን ስም ባነገበው ሠራዊት እና በእነ ጄኔራል ፣ ኮሎኔል ወዘተ ብቻ አይደለም ገና እነ ፊታውራሪ ደጃዝማች ግራዝማች እያሉ ጀምሮ ከሩቅ ሆኖ በሚተኮስበት ወቅት ሳይሆን መሣሪያ እስከ አፍንጫቸው በታጠቁ ዘመንኛ ሠራዊት በጦርና በጎራዴ ገጥሞ ሀገር ድንበር ርስት ባስጠበቀውም ጭምር ነው እንጂ በመሐልም የመርዝ ጋዝ እየዘነበበት እንዲሁም ከጎረቤትም ለመናገሻ ከተማዋ አዲስ አበባ በቅርብ ርቀት እስኪከትሙ ድረስ ሀገር መሬት ውስጥ ገብተው የወረሩንንን በመመከት ነው እናም አጠቃላይ የኢትዮጵያ ሠራዊት በዓል ቢሆን እመኝ ነበር ግን የአሁንና የአሁን ብቻ መሆኑ አሳዝኖኛል፡፡
ታሪኮቹም ሁሉ የሚወሩት የሚወሱት ሁሉ በጣም በሚገርም ሁኔታ የአሥራ ስምንትና የሃያ አመት ታሪክ ነው፡፡ ለምን የቅርብ ታሪክ ቀረበ የሚል ሀሳብ የለኝም ግን ሁሉም ነገር የሚነሳው ስለ ‘ለውጡ’ ትውልድ ብቻና ብቻ ነው፡፡ ለውጡ ተሳክቷል ወይስ ጠፍቷል የሚለው ተጨማሪ ክርክር ቢፈጥርም ማለቴ ነው፡፡ ይሄ ግን በምንም መለኪያ ትክክል ሊሆን አይችልም ፡፡ ነባሩም ፣ የተገለለውም ፣ ያለውም ፣ ያለፈውም መታወስ አለበት ምክንያቱም የኢትዮጵያ ታሪክ በሺዎች እንጂ በአሥራዎች የሚቆጠር ስላልሆነ፡፡ እናም ከምንም ነገር ተነስተን የሃያ ዓመታት ታሪክን እንደ ሙሉ ታሪካችን ደጋግመን በጆሯችን ስንሰማ ከባድ ቅሬታ እየተሰማን ነው፡፡
በነገራችን ላይ የሃያውም ዓመታት ታሪኮች እንዳሉ የአንድ ብሔርን ማንነት እና ልፋት ልዕልና ብቻ የሚያሳይ ነው፡፡ እውነት ግን ሌሎቹ አልታገሉም ? ታለዋል እንጂ ያውም የታገሉትም ገዢው ፓርቲ እንደሚለው አንዳንድ ጥቅመኞችን ሰብሰብ አድርገው ይሄኛውም ታግሏል ብለው የነሱ ሎሌዎች በማድረግ እጆቻቸውን ለማስረዘም በተደረገው ሴራ ሴራ ዓይነት ዓይደለም ፡፡ ደግሞስ ቆይ እነ ኢህአፓ ፣ ኢዲዩ የመሳሰሉት ለሀገር መስሎኝ የታገሉት እንጂ ለነጮች ተሸጠው ወይም ሀገራቸውን ለማስረከብ አይደለም እንደኔ እንደኔ፡፡ ቀድመዋል ለመጀመርም ቢሆን ነገር ግን በአንዳንድ ምክንያቶች ከሜዳው ተገለዋል አንዳንዱም ታፔላውን ቀይሮ ወደዚህ ተጠምዝዟል፡፡ እነጋሼ ከመጀመሪያውም አንድ ሀገር ብለው አልተነሱም አሁንም አያስቡም ስለተመቻቸው ነው ቦታውን ያደላደሉት፡፡ ነገር ግን  የኢትዮጵያ ህዳሴ መንገድ ፈር ቀዳጅ ሆነው አረፉት፡፡ የታሪክ ንጥቂያ ከባድ ነው፡፡ ያውም ለመበታተን የተነሳ ኃይል አሁን ደግሞ የአንድነት ሰባኪ እንዴት ይሆናል፡፡
ይሁን ምናልባትም በሕይወት ተምሯል ተብሎ ሲታለፍ ፡፡ የሚናገረው የሚሰራው ነገር ሁሉ ተምታቷል፡፡ ሕብረ ብሄራዊነትን ያነገበ የመከላከያ ሠራዊት ተብሎ ይለፈፋል፡፡ ነገር ግን እሳቱ ላይ የሚጠበሱት ሠራዊቶች ሁሉም ሊባል በሚችል ደረጃ ከሌሎች ክልሎች የተውጣጡ ይሆኑና ወይ ለግምገማና ወሬ ለማቀበል ታማኝ ስለሆኑ ብቻ አብረዋቸው የሚሆኑ ካልሆኑ በስተቀር ሁሉም አመራር ላይ ያሉት የአንድ ብሔር አባላት ናቸው ለነገሩ የተነሳንበት ጉዳይ እንደነሱ አጠራር ‘የፌደራል መከላከያ ሰራዊት ቀንን’ በማስመልከት ስለሆነ ነው እንጂ ሁሉም ቦታ እነሱ ብቻ ናቸው፡፡ ልክ እንደዚህ ዓይነት ጉዳይ ሲነሳ ኢነተርሃምዌይ ይሉናል፡፡ ነገር ግን እራስን ከሌሎች ነጥሎ የጥቅም አደላዳይ እና ብቸኛ ተጠቃሚ ከመሆን የበለጠ ኢንተርሃምዌይነት አለ እንዴ? በጥያቄ ይደር፡፡
ይህ እንዳለ ይቆይና ስለ አውደ ርዕዩ ትንሽ ልበል፡፡ ጉብኝቱ መልካም ነበር ግን ብዙ የጠበቅነው ነገር አልሆነም ወታደራዊ ሰልፎች፣ ፓራኮማንዶ ትርዒት፣ ተሻሻሉ የተባሉትም መሣሪያዎች በዛ ብለው ቴክኖሎጂዎቹም በተቻለ የመገጣጠም ሥራ ሳይሆን ከአንድ ምርት ቢያንስ አንዱን ክፍል እዚሁ ለማምረት ጥረት ቢደረግ፡፡ ሌላው ደግሞ ብረታብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን ሲቋቋም የግሉ ዘርፍ ሊደፍረው የማይችለውን የኢኮኖሚና የኢንዱስትሪ ዘርፍ ለማንሳት ለማጠንከርና ለማበርታት ነው የሚል ነበር ግን አሁን ተራ የሚባሉ የፕላስቲክ /ተራነታቸው ሌሎች የግል ድርጅቶች የገቡበት ንግድ ስለሆነ/ ኤሌክትክ ሽቦ እና የመሳሰሉትን እናመርታለን ሲሉ ቅር ብሎኛል፡፡ እንዲሁም አንዳንዶቹ በቅርበትም የማውቃቸው ምርቶቻቸው ውጤታማ አልበሩም እነሱን ውጤታማ እንደሆኑ አድርጎ የማቅረብ የመሳሰሉት ነገሮችና ሌሎችም መታረም አለባቸው፡፡ ነገር ግን ለቴክኖሎጂ ሽግግር የሚያደርገው ጥረት ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ ምክንያቱም አሁን በዓለም ላይ እንደ መርህ የምንጠቀምባቸው ጽንሰሀሳቦች አብዛኛው የተገኙት ከወታደራዊ ሳይንስ ጠበብቶች ነው፡፡
እንደማጠቃለያ መቼም ቢሆን ደምና አጥንት ለከፈሉ አባቶቼና እናቶቼ እህት ወንድሞቼ አመራርም ሆናችሁ የበታች ምስጋናዬ የላቀ ነው፡፡ ለገዚው ፓርቲም ቆም ብላችሁ አስተውሉ ሁልጊዜም ምርጫ 97 መጥቶ አሁን ነው የገባን እያላችሁ አትሸውዱን ጊዜ ሰጥቶ ህዝብ አዳምጡን ሲላችሁ አንደበታችሁን ቆጠብ አድርጋችሁ ጆሯችሁን ዘርጋ አድርጉት፡፡ ብዙ ትምህርት ይገኛል አይዟችሁ አትናቁት፡፡ ምናልባት መሳሪያ አልታጠቀ ሊሆን ይችላል ግን ቀን ይፈታዋል የናንተን መሣሪያ፡፡ ልብ በሉ ሁሉንም አድራጎታችሁን ሕብረ ብሔራዊ አድርጉት የጎጠኝነት ፖለቲካችሁ እዛው ጫካው መልሱት ፡፡ ወይንም እናንተ ጫካ ተመለሱና …….

Sunday, February 3, 2013

የዘመኑ ሽለላ


መቼም አንባቢዎቼ ሁሉ ምን ዓይነት ዘመንኛ ሽለላ ተገኘ ሊሉ ይችላሉ፤ ቢሆንም ደግሞ አልፈርድባቸውም፡፡ ምክንያቱም አሁን አሁን ዘመናዊ ነገር ዘመናዊ ፈጠራ እየተባለ ከማዳነቅ ውጪ ድሮ የነበርንበትን አይተን መነሳት ተስኖናል፡፡ ከባዶ /ዜሮ/ ወለል ላይ እየተነሳን ሩቁ እየራቀን ሁሌም ማንነትን ማንቋሸሽ ሆኗል ሥራችን፡፡ ምናልባትም አባቶቻችን በደረሱበት ደረጃ ላይ ብቻ እንኳን ተነስተን ብንጀምር እራሳችንን ዓለም አሁን ያለበት ቦታ ላይ ነው የምናገኘው፡፡

የጽሁፌ መነሻ ሐሳብ ይሄ አይደለም ለነገሩ ግን ሁሌም የነበርንበትን ማስታወስ መልካም ነው በሚል ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ አሁን ባለንበት ዘመን ፉከራው ሽለላው ሁሉ ገንዘብ ከማግገኘት ጋር በጣም የተቆራኘ በመሆኑ ስልምንነጋገርባቸው ቁሶችም ሆነ ቅርሶች ማኅበራዊም ሆነ ባህላዊ እንዲሁም መንፈሳዊ ፋይዳ ማሰብ ተስኖናል፡፡ ወይም ላለማሰብ እራሳችንን አዘጋጅተናል፡፡
በሀገራችን ብቸኛውም አንጋፋውም የመንግስትም የፓርቲም የቴሌቪዥን ጣቢያ በዚህ መልኩ የተካነ ነው፡፡ በሥሩ ያሉ ሠራተኞችም እንደ ድርጅታቸው መካን ግድ ይላቸዋል፡፡ እዚህ ላይ አንባቢ ልብ ሊልልኝ የምፈልገው ነገር ግድ ይላቸዋል እንጂ ናቸው አላልኩኝም ምክንያቱም አንዳንድ ጊዜ እፍንፍን አድርገው መናገሪያ መስመር ያበጁልሃል እናም ከዚያ በላይ መሻገር የቴሌቪዥን ጣቢያውን ፖሊሲ መንካት ቀይ መስመር ማለፍ ነው እናም የተሰጣቸውን ክበብ ይዘው እንደ ዘይት ጨማቂ ግመል ይዞራሉ ነገም አሁንም ትላንትም አንድ ዓይነት ዘገባ አንድ ዓይነት ድርጅት ፡፡

በተለይ አንባቢዎቼ የመንግስት ወይም የመንግስት የልማት ድርጅቶች ውስጥ የሚሠሩ ከሆነ ወይም መረጃው ካላቸው በጣም ይረዱኝ ይሆናል፡፡ ሚኒስትሩ አሉ ከተባለ የማይፈጸም የማይወርድ ትዕዛዝ የለም የትኛውም ሚኒሰቴር እንደሆነ የማረጋገጫ ጊዜ እንኳን የለም በለው ነው፡፡

ማንኛውም ዓይነት ስብሰባ ሲዘጋጅ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ተብሎ ከስብሰባው አጀንዳ ቀድሞም ቢሆን ቢነሳ አይገርምም፡፡የውጪ ሀገር ዘፋኞችም ሲመጡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ለሀገሪቱ የሚሰጠውን ዓለም አቀፍ ሽፋን በተመለከተ ሰፊ ዘገባ ቢቀርብም እንዲሁ፡፡ ነገርግን አንድ ባሕላዊ ስነስርዓት ወይም ኃይማኖታዊ በዓልን ድምቀት ለመስጠትም ሆነ የቱሪዝም ገበያ ለማግኘት ያለውን ጥቅምና ትርጉም ወደኋላ ማለት ከስህተትም እንደአባቶቻችን አባባል ነውር ነው፡፡ ወደኋላ አላልንም እንደሚሆን ማስተባበያው እጠብቃለሁ፡፡ እንግዲህ አሁን አሁን በጣም ሲበዛ እያየሁት እያስተዋልኩት የመጣሁትና ከጊዜ ወደጊዜ እየባሰበት የመጣ ነገር ቢኖር ይሄ በመሆኑ ነው ስለዚህም ልጽፍ የተነሳሁት፡፡ ይህንን ሀሳብ ስጽፍ በጉራጌ ዞን አንድ አካባቢ ከዋሻ ውስጥ ተቆፍረው የወጡ ኃይማኖታዊ ቅርሶችን የሚያሳይ ዘገባ እየቀረበ ነበር፡፡ መቅረቡ ባልከፋ /የዘገባ ሽፋን ሊባልነው እንግዲህ/ ግን ከተገኘው የመንፈሳዊ ሀብትነት አንድም ነገር ሳይባል /የሕዝቡ ነኝ በሚል ጣቢያ/ ስለ ቱሪዝም ሀብትነቱና ስለገቢ ማመንጫነቱ ሲነገር ስሰማ ገረመኝ ይህንን የተናገሩት አንድ ካህን ናቸው ግን ይህ ምላሽ ለተሰጣቸው ጥያቄ መሆኑ አያጠያይቅም ሌላው ደግሞ የፈለጉትን ሀሳብ ብቻ ቆርጠው እንዳቀረቡት ምንም ጥያቄ የለውም ለማን ነው ሌላው ጥያቄ የተጠየቀው ለእኛ ለህዝቡ አይደለም እንዴ፡፡ በነገራችን ላይ ከዚህ በፊት የሰማሁት ቢሆንም በታሪክነቱ ተቆፍረው ከወጡት ቅርሶች ውስጥ አንዱ ጥንት አባቶቻችን ዘመንኛው ብዕር ሳይሰራ በፊት ቀለም በውስጡ ተንቆርቁሮ መጻፍ የሚያስችል ብዕር ነበረበት አባቶቻችን በጣም ጠቢብ ነበሩ ልብ በሉ ጠባብ አላልኩም፡፡

ይሄም ይቅር በክልል ቴሌቪዥን የቀረበ ዝግጅት ነው ብለው ይለፉት በደቡብ ክልል ቴሌቪዥን ስለቀረበ፡፡ ነገር ግን የመስቀልን ደመራና የጥቀትን በዓል ማክበር መጀመሪያ መንፈሳዊ ዋጋው ተከፍሎት በትርፉ የቱሪዝም ትርፍ ቢያገኙበት ይሻላል፡፡ መቼም ሽልማት በዚህ ዘመን በምን እንደሚሰጥ ግራ ያጋባል ብቻ ግን ሆነም ቀረም ከተሸለሙት ጋዜጠኞቹ መካከል ጥምቀት እንደካርኒቫል ዓይነት ነው ብለው የሚናገሩም አልጠፉም፡፡ እንደው እውነት እንነጋገር ከተባለ ለአንድ ኢትዮጵያዊ ራቁት ዳንስ የሚደነስበትን ስነስርዓት ከመንፈሳዊ በዓል ጋር ማነጻጸር አማርኛ ማወቅ ነው ወይስ ….. ምናልባት በባሕላችን ከሚዘወተሩት አባባሎች ውስጥ ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ እና የተያያዙት ነው የሚያስታቸው እንዳይባል የሚሸለም ሰው አጣርቶ እና አጥንቶ ነው የሚናገረው፡፡ ይህ ከላይ የጠጠቀሰው አባባል አንደኛ ታቦት ስለሚወጣ ስለታቦቱ ክብር ሁለተኛ ሰው ግልብጥ ብሎ ስለሚወጣ ትዳር ከእግዚአብሔት ነው የሚገኘውና ለሕይወት አጋርነት ለመምረጥ እንዲሁም ጥምቀት የመታደስ በዓል ስለሆነ ተያይዞ የሚመጣ ነው እንጂ እንደተባለው ዓይነት መነጻጸሪያ የሚገባው አይደለም፡፡

ሁልጊዜም ዘገባው በድምቀት ተከበረ ከተባለ በኋላ ሀገሪቱ ከቱሪዝም የምታገኘውን ገቢ ያሳድጋል ይባላል፡፡ በቃ፡፡ እንደኔ እንደኔ ግን ብዙ ሊባልለት የሚችለውን በዓል አከባበራችንን ከሚባልለት ቀንሰን መንፈሳዊና ባሕላዊ ዋጋውን በመቀነስ ለቁሳዊ ጥቅም ማዋል ስህተት ነው፡፡ ይልቅ ዓይናችንን የሚያሳምሙንን ጆሮአችንን የሚያደነቁሩንን በይዘታቸውም ሆነ በቅንብራቸው የማይመጥኑ ዘፈኖችን አጣርተው እዲያቀርቡ ዝግጅቶቻቸውን እንዲፈትሹ /ባያደርጉትም ብሄራዊ ግዴታችን ነው ለበለጠ ለውጥ አስተያየት መሰጣጠት/ አሳስባለሁ፡፡ ካልሆነ ግን ዝግጅቱ መስጦን ሳይሆነ ስለሀገራችን ሁኔታ ማየት ማዳመጥ የምንፈልግ ዜጎችን እያሰላቻችሁ ነውና እባካችሁ እላለሁ፡፡

Wednesday, March 21, 2012

በማንኛውም ነገር እንማር


በሕይወታችን ሁልጊዜም አንድ ዓይነት መልስና መንገድ ብቻ ያለ የሚመስለን ሰዎች በብዛት ተሳስተናል ፡፡ ነገር ግን ብዙ ማስተዋል ያለብን ነገር አለ ፡፡ ወደዚህ ምድር ስንመጣ ያለምክንያት እንዳልመጣን ሁሉ ስንኖርም በዙሪያችን የሚያጋጥሙን ነገሮች ሁሉ ያለምክንያት አይደለም፡፡ 
በነገራችን ላይ እኔ ይሄንን ጡመራ ስጀምርም ብዙ ጊዜ ሀሳቤን እንድገልጽባቸው የምፈልጋቸውና ሳስተውላቸው መታረም ይገባቸዋል ብዬ የማስባቸውን ጉዳዮች በግልጽ መናገር እና መጻፍ እፈልግ ነበር ግን ተናጋሪ ብቻ ለመሆን አይደለም በተቻለ አንባቢም ለመሆን ነው ፡፡ ስለዚህም ከዚህ በኋላ የምጽፋቸው ጽሁፎች ሁሉ የሚያጠነጥኑበት መንገድ ሁሉ በሀገር ጉዳይና
በአጠቃላይ የሕብረተሰባችን ሁለንተናዊ ዕይታዎች ላይ ይሆናል ፡፡
ስለዚህም በመግቢያዬ ላይ እንደገለጽኩት ሀገር የምትመራው በፖለቲከኛ ብቻ አይደለም፡፡ ዕድገት የሚመጣው በመንግስት ብቻ አይደለም፡፡ ሕዝብም ሁልጊዜ ጠያቂ እና ጣት ጠቋሚ አይደለም፡፡ መንግስትም ጠረጴዛ ላይ ቁጭ ብለው ያሰቡት ብቻ ውጤታማ ነው ብሎ ማሰብ ትክክል አይደለም፡፡ ስለዚህም ከሕዝቡ በተለያዩ መስኮች የሚመጡ ግብዓቶችን በአስተዋይነት መንገድ መከታተልና ማዳመጥ፡፡ ሕዝብም የሚደረገው ሁሉ እርኩስ ነው ሁሉም ቅዱስ ነው ብሎ ከማመስገንና ከማማረር የጭፍን አካሄድ መላቀቅ አለብን፡፡
የምናስበውና የምንነጋገረው ሁሉ ለሀገራችን የነገ ተስፋ እና ዕድል ወሳኝ መሆኑን በመገንዘብ የጠበበ ዕይታዎቻችንን ቀን በቀን በማስተካከል እና ለማዳመጥ በመዘጋጀት መስተካከል አለብን ፡፡ ልጆቻችን ወደየት እየሄዱ ነው ሳይሆን ጥያቄው ምን ዓይነት ስነምግባር መገብናቸው ፣ ምን ያህል ዕድል ሰጠናቸው ፣ ምንያህል እኛስ ለመቀበል መሠረታዊ ዝግጁነት አለን የሚለው መመለስ አለበት፡፡ ምክንያታዊ የሆነ ነቀፋ እና ድጋፍ ለማድረግ እራስን ከዛሬ ጀምሮ ማዘጋጀት አለብን፡፡
ዕውቀቶቻችን ሁሉ ለጋራ ጥቅም መዋል የማይችሉ ከሆነ ከንቱ ናቸው፡፡ እዚህ ላይ ግን ማንም ሰው ስለተማረ ስለራሱ ማሰቡን ትቶ ስለሰው ብቻ ያስባል ወይም ማሰብ አለበት ማለቴ እንዳልሆነ አንባቢ ይገንዘብልኝ፡፡ ዕውቀት ሥራ ላይ ዋለ የሚባለው ለሽያጭ ሲቀርብ መሆኑ አይካድም ሽያጩ የንዋይ ልውውጥ ይኑረውም አይኑረውም፡፡ ለሽያጭ ቀረበ ማለት ደግሞ ለሕዝብ ጠቀሜታ እና ዕይታ ዋለ ማለት ነው ስለዚህም በማንኛውም መንገድ ለሕዝብ ጠቀሜታ የዋለ አገልግሎትም ሆነ ቁሳዊ ምርት መና መሆን የለበትም፡፡ ዘመን ተሻጋሪ አስተሳሰብና ተግባር ማራመድ አለብን፡፡ ዛሬ በደመ ነፍስ ተናግረን ነገን መልስ የሌለን ወይም የሚያስወቅሰንን ነገር መፈጸም የለብንም፡፡ ለዚህም ነገን እያሰብን መሥራቱ ተመራጭ እና የአስተዋይት ውጤት ነው፡፡

ሁልጊዜም በጎ በጎውን ማሰብ መልካም ነው ነገ መልካምነታችን ዋጋ ይከፍለናል